ኢመደአ ከውጭ ጉዳዩ ኢንስቲትዩት ጋር በጋራ ለመስራት የሚያሥችል የመግባቢያ ሰነድ ተፈራረመ
ኢመደአ ከውጭ ጉዳዩ ኢንስቲትዩት ጋር በጋራ ለመስራት የሚያሥችል የመግባቢያ ሰነድ ተፈራረመ
የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር (ኢመደአ) የውጭ ጉዳይ ኢንስቲትዩት ጋር በጋራ ለመስራት በሚያስችላቸው በአቅም ግንባታ፣ በሳይበር ዲፕሎማሲ እና በጥናትና ምርምር ዘርፎች ላይ የመግባቢያ ሰነድ ተፈራረሙ፡፡
በፊርማ መርሃ-ግብሩ ላይ የተገኙት የኢመደአ ዋና ዳይሬክተር የተከበሩ አቶ ሰለሞን ሶካ ኢመደአ በዋናነት የኢትዮጵያ የሳይበር ደህንነት ሉዓላዊነት ከማስከበር እና የቴክኖሎጂ ባለቤትነት ከማረጋገጥ አንፃር ሀገራዊ ፋይዳ ያላቸው ስራዎች እየሰራ መሆኑ ገልፀዋል፡፡
ዋና ዳይሬክተሩ የተከበሩ አቶ ሰለሞን እንዳሉት የሳይበር ደህንነት ምህዳሩ ተለዋዋጭነት፣ ኢ-ተገማች እና ደንበር የለሽ ከመሆኑ አንፃር ከብሄራዊ ደህንነትና ከውጪ ጉዳዮች ፖሊሲና አጀንዳዎች ጋር በማስተሳሰር በሳይበር ዲፕሎማሲ ላይ ጥናትና ምርምሮች መስራት አንዱ የአስተዳደሩ ቁልፍ አጀንዳ እንደሆነ ጠቅሰዋል፡፡
የሀገርን ብሔራዊ ጥቅም ከማስጠበቅ አንፃር ከውጭ ጉዳይ ኢንስቲትዩት ጋር በሳይበር ዲፕሎማሲ ከሚሰሩ የጥናትና ምርምሮች ጎን ለጎን ኢንስቲትዩቱ በኢመደአ የለማ ደህንነቱ የተጠበቀ ቴክኖሎጂዎች እንዲጠቀሙ እንደሚያደረግ ዋና ዳይሬክተሩ ተናግረዋል፡፡
አያይዘውም የመግባባቢ የስምምነት ሰነዱ በዚህ እንደማይገደብ ያነሱት ዋና ዳይሬክተሩ በቀጣይ የድርጊት መርሃ ግብር ወጥቶለት ሙሉ በሙሉ ወደ ትግበራ እንደሚገባም አስታውቀዋል፡፡
የውጭ ጉዳይ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ዶ/ር ደሳለኝ አንባቸው በበኩላቸው ኢንስቲትዩቱ በፀጥታ፣ በዲፕሎማሲ እና በሰላም ጉዳዮች ላይ በሚያደርገው የጥናት እና ምርምር ስራዎች ከኢመደአ ጋር በጋራ መስራቱ ትልቅ አቅም እንደሚፈጥርላቸው ጠቅሰዋል፡፡
ሁለቱም ተቋማት ሀገራዊ ጥቅምን ማስጠበቅ አንኳር ግባቸው ነው ያሉት ዶ/ር ደሳለኝ በዚህም ትርጉም ያለው ሀገራዊ ፋይዳ ያላቸው ብዙ ስራ መስራት እንደሚቻል ገልፀዋል፡፡
በመግባቢያ ሰነዱ ላይ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ግብዓት እንደሰጠበት የጠቀሱት ዶ/ር ደሳለኝ በአጠረ ጊዜ ውስጥ ወደ ትግበራ እንደሚገባም አስታውቀዋል፡፡